‹‹Leadership is Falling in Love with the People You Lead or Serve››
(ቀድሞዋ የማላዊ ሴት ፕሬዝዳት ጆሴ ባንዳ)
ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነኝ ከትናንትና በስቲያ ከሥራ ወጥቼ ወደ ቤቴ ለመሄድ በተሳፈርኩበት ሃይገር ባስ ውስጥ ያጋጠመኝ እጅጉን ያሰዛነኝ ክስተት ነው፡፡ በተሳፈርኩበት ሃይገር ባስ ውስጥ ወጣቱ ሹፌር የይሁኔ በላይን የአገር ባህል፣ ሞቅ ያለ የበዓል ዘፈን እስከ ጣራው ለቆታል፡፡ ነገሩ ግራ አጋባኝ፡፡ በጉዞአችን መካከልም በአይ ኤስ ታጣቂዎች በግፍ የታረዱት ኢትዮጵያውያን መሆናቸው ገና አልተጣራም በማለት ሲያንገራግር የነበረው መንግሥት ዘግይቶም ቢሆን የተሠዉት ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን አምኖ መግለጫ አውጥቷል፡፡ ታዲያ ይህ ሰው በዚህ ኢትዮጵያችን የኀዘን ከል በለበሰችበት የሰቆቃና የዋይታ ቀን ምን ቢሰማው ነው ይህን ዘፈን እስከ ጣራው ከፍቶ እያስጮኸው ያለው ስል ራሴን ጠየኩኝ፡፡
ይህ ሰው ጤነኛ አይደለም ወይስ … የሹፌሩ ነገረ ሥራው እጅጉን ቢከነክነኝ ዞር አልኩና ወንድሜ ይቅርታ ኀዘን አይደለም እንዴ ምናለ ዘፈኑን ብትዘጋው አሊያም ለራስህ ብቻ ብታዳምጥ አልኩት፡፡ መለስ አለና የምን ኀዘን አለኝ ፈርጠም ብሎ፡፡ ነገሩ ግራ አጋባኝ ይህ ሰው በኢትዮጵያ ምድር አይደለም እንዴ ያለው ስል በመጠራጠር ቀና ብዬ አየሁት፡፡ እንዴ ወንድም በደቡብ አፍሪካና በሊቢያ በግፍ የሞቱት፣ የተሠዉት ወገኖቻችን የእኛ ወንድሞች፣ የእኛ ወገኖች አይደሉም፣ ይህ ኀዘን የሁላችንም ኀዘን አይደለም እንዴ አልኩት ንዴትም እልክም በተቀላቀለበት ድምፅ፡፡
ወጣቱ መለሰና እኛ ታሪክ አናወራም፡፡ ወደፊት ነው የምናስበው፣ ልማት ነው የምናልመው አለኝ፡፡ እንዴ ታሪክ እኮ አይደለም ወንድሜ … አላስጨረሰኝም … በዚህ ሰው ምላሽ ድንጋጤም፣ ንዴትም ይንጠኝ ጀመር፡፡ ከዚህ በላይ ላነጋግረው አልፈለኩምና በእፍረትና በንዴት መካከል ውስጥ ሆኜ ፊቴን መለስኩ፡፡ ኢትዮጵያዊው መተዛዘናችን፣ ያ ከወንድሜ በፊት እኔን ያስቀድመኝ የሚለው ድንቅና አኩሪ ባህላችን የት ገባ አልኩ ለራሴ በለሆሳስ፡፡ ወደየት እየሄድን ነው ስልም ራሴን ጠየኩ፡፡
አፍታ ቆይቼም ይህ ወጣት የዘመኑ ልማታዊ ሹፌርና በአብዮታዊ ዲሞክራሲን የተጠመቀ ጭፍንና መደዴ ካድሬ መሆኑ ሲገባኝ ደግሞ ፍቅርንና ሰብአዊነትን ለተራቆተው ግልብ ማንነቱ አዘንኩለት፣ አፈርኩለትም፡፡ ለሰው ልጆች፣ ለሚያስተዳድረው ሕዝብ ፍቅርና ክብር፣ ሰብአዊነትና ርኅራኄ የተለየው መንግሥታችን እንዲህ ዓይነቶቹን የሰው ሽታ የሌላቸውን የልማት አርበኞች ወይም ካድሬዎች በገፍ እያፈራልን ነውና የነገ ዕጣ ፈንታችን ሲታሰበኝ ለራሴም ለምስኪን ሕዝቤም አዘንኩ፡፡
ለመሆኑ የሆነስ ሆነና ሰብአዊነትን ማዕከል ያላደረገ ልማትስ ጠቀሜታው ምን ድረስ ነው፣ እስከየትስ ነው ሊጓዝ የሚቻለው፡፡ የአገራችን የልማት አጀንዳ እንዲህ ፍቅርን፣ ሰብአዊነትንና ርኅራኄን አሸንቀጥሮ የጣለ ጎዶሎ መሆኑን ሳስብ ደግሞ ይባስኑ ፍርሃቴና ኸፍረቴ ጨመረ፡፡
ለነገሩ ይህ ልማታዊ ሹፌር አይፈረድበትም፡፡ መንግሥትስ ጠላቶቻችን ሳይቀር የመሰከሩትንና እንደ አሜሪካ ያሉ ወሬ የሚያነፈንፉና መረጃ የማያመልጣቸው ኃያላን አገራት ሣይቀሩ በአይ ኤስ በግፍ ታርደው ሰማዕት የሆኑት ወገኖቻችን ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን አገረጋግጠው የኀዘን መግለጫ የላኩበትን የሕዝባችንን መርዶ አምኖ ለመቀበል እንዲያ ሲያንገራግር ታዝበነው የለ፡፡ ይህን ዘግናኝ የሆነ ዜና የዓለም መገናኛ ብዙኃን ሁሉ እየተቀባበሉ ለሁሉም እያደረሱ ባለበት ሰዓት መንግሥት እነዚህ በግፍ የታረዱ ሰዎች ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን ገና አላረጋገጥንም ሲል ነበር በግልጽ የተናገረው፡፡
ዘግይቶም ቢሆን ይህ ዘግናኝ እልቂት የደረሰባቸው ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን መሆናቸውን አምኖ የተቀበለው መንግሥት መላው ሕዝባችን በኀዘን ድባብ ውስጥ ገብቶ እምዬ ኢትዮጵያም በደቡብ አፍሪካ፣ በየመንና በሊቢያ በግፍ ለወደቁባትና ለተሠዉባት ልጆቿ የኀዘን ማቅ ለብሳ በምታነባበት የዋይታ ቀናችን መንግሥት ወንድማችን ዲ/ን ዳንኤል እንዳለው፡- ‹‹ምንም ሰብአዊ ስሜት የሌለበት፣ ማዘን መደሰታቸውን የማይገልጽ፣ ሰው ሰው ማይሸት መግለጫቸውን አስተላለፉልን፡፡ ጥልቅ ኀዘናችንንም ያለ ምንም እፍረት የተራ ፕሮፓጋንዳቸው ማስፈጸሚያቸው አደርገውት አረፉት፡፡
ሕዝቡ ከልቡ አዝኖ በየቤቱ፣ በየጓዳው በእንባ እየታጠበት ያለውን መርዶውን፣ ጥልቅ ኀዘኑን መንግሥት በይፋ እስኪገልጸው በሚል ሰበብም በአገሪቱ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያና በኤፍ ኤም ሬዲዮኖቻችን ምንም እዳልተከሰተ ሁሉ የአስረሽ ምቺው ዘፈኖችና በንግድ ማስታወቂያቸው ልባችንን ሲያደሙት፣ ጆሮአችንን ሲያመግሉት ነበር የዋሉት፡፡ በዚህ ለሕዝባችን የዋይታና ሰቆቃ በሆነበት ቀን ‹‹የምን ኀዘን ነው የምን ትካዜ፣ ሁሉም ያልፋል በጊዜው›› የሚል በዋይታችንና በሰቆቃችን ቀን እንዲህ ዓይነት ኢ-ሞራላዊና ሰብአዊነት የጎደላቸው ዘፈኖችን በማሰራጫ ጣቢያዎቻቸው የለቀቁ የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎቻችን በእውን ለሰው ልጆች ፍቅር፣ ሰብአዊነትና ርኅራኄ አላቸው ብሎ ማለት ይቻላልን?!
ኢትዮጵያዊነት እንዲህ ወርዷል ማለት ነው፣ መተዛዘንና መተሳሰብስ በኢትዮጵያችን ምድር እንዲህ በጠራራ ፀሐይ ውኃ በልቶታል ማለት ነው?! በዚህች ምስኪን አገርስ ሃይ ባይ መሪ፣ መካሪና ዘካሪ የሃይማኖት አባትና የአገር ሽማግሌ የለንም ማለት ነውን?! በእጅጉን ያሳዝናል፣ ልብንም ይሰብራል!!
በደቡብ አፍሪካ፣ በየመንና በሊቢያ ያለቁ፣ በግፍ የታረዱ ያሉ ወገኖቻችን አይደሉም እንዴ! ምንም ዓይነት ኢሰብአዊነትና ጭካኔ ነው?! በየቤቱ በስደት ከጉያቸው የወጡ ልጆቻቸውን ዕጣ ፍንታ በማሰብ በኀዘን ተኮራምተው፣ በዋይታና በሰቆቃ ውስጥ ለገቡ ምሰኪን እናቶችስ እውን የመገናኛ ብዙኃኖቻችን ስትለቁት በነበረው የአስረሽ ምቺው ዘፈኖቻችሁና የንግድ ማስታወቂያዎቻችሁ ምን መልእክት፣ ምን ዓይነት ምሥራች ነው ልታስተላልፉላቸው የፈለጋችሁት?! በእውነት አፍረንባችኋል፡፡
ይህን ውሎዬን ሲየንገበግበኝ የዋለውን የመገናኛ ብዙኃኖቻችንን ነገረ ስራ እብከነከነኝ ኀዘኔንና ብሶቴን በውስጤ እንደተሸከምኩና በሃይገር ባሱ ሹፌር ሁኔታ እየተገረምኩ ቁጭቴንና እልኬን በውስጤ አምቄ ወደ ቤቴ ደርስኩ፡፡ በመኝታዬ ክፍል ከጥቂት እረፍትም ካደርኩ በኋላም በደረሰባት የመኪና አደጋ የተነሣ በቤቷ የተኛችውን ጓደኛችንን ለመጠየቅ ከአንድ ጓደኛዬ ጋር ወደ ቤቷ አመራን፡፡ ጓደኛችንንም እንኳን እግዚአብሔር አተረፈች በማለት ጤንነቷ አሁን እንዴት እንደሆነ እየጠየቅናት ስንጨዋወት በነበረበት ሰዓት የዚህች ጓደኛችን አከራይ ለጥየቃ መጣች፡፡
ሰላምታ ተለዋውጠን ጓደኛችንን በጋራ ሆነን እያጽናናናትና እንድትበረታም እየነገርናት የሁሉም ሰው መነጋገሪያ ጉዳይ ወደሆነው በደቡብ አፍሪካና በሊቢያ በወገኖቻችን ላይ ስለደረሰው እልቂት ማውራት ተጀመረ፡፡ በመንግሥት የዘገየና ግራ በሚጋባው የኀዘን መግለጫ የበገነው ጓደኛዬም፡- ‹‹መንግሥት ዘግይቷል፣ ተግባራዊ ዕርምጃ መውስድ ይገባዋል፡፡›› በማለት ለጓደኛችን አከራይ ብሶቱንና ንዴቱን ዘረገፈላት፡፡ ይህች ሴትም ኖ ኖ ኖ መንግሥት እኮ ማጣራት አለበት፣ ዝም ተብሎ መግለጫ አይወጣም፡፡ እንደምታውቁት በሊቢያ ኤምባሲ የለንም መንግሥት በግብጽ አገር ባሉት አምባሳደራችን በኩል እስኪያጣራ ድረስ ነው የቆየው እንጂ ብዙዎች እንደሚሉት …፡፡
ይህች ሴት ንግግሯን ፕሮፓጋዳዋን ማለት ይቀላል በፍጥነት ቀጠለች፡፡ ይህ በፌስ ቡክ በስሜታዊነት አስተያየት እየሰጡ የሚገኙ ሰዎች ትክክል አይደሉም ስትልም ፈረደች፡፡ በእጇ የያዘችውን እጅግ ውድ የሆነ ስማርት ስልኳን እየከፈተችም ማብራሪያዋንም፣ መግለጫ ማለቱ ሳይቀል አይቅርም ያለ ምንም ከልካይ ታዘንብብን ጀመር፡፡ የፖለቲካ ሳይንስ ምሩቅ እንደሆነች በመግለጽም ስለ ዲፕሎማሲ፣ ስለ ጦርነት፣ አክራሪነት፣ ሽብረተኝነት ትርጉሙን በቅጡ የማታውቀውን የእንግሊዝኛ ቃላትን ያለ ቦታው በመደንጎር ልታስረዳን ሞከረች፣ ብዙ ጣረች፡፡
ወሬዋ ማባሪያ፣ ማቆሚያ ያለው አይመስልም፡፡ በእውቀትና በእውነት ላይ ተመሥርታ ሣይሆን በጥራዝ ነጠቅ ባገኘችው በስማ በለውና እዚህም እዛም በቀራረመችው እንቶ ፈንቶ ወሬዋ እንዲህ ስትራቀቅብን ሳያት ከልቤ ታዘብኳት፡፡ እዚህች አገር ላይ ‹‹ሀብተ ድፍረትንና ሀብተ ንቅትን የታደሉ›› ጸሐፊያንና አዋቂ ነን ባዮች በዝተዋል የሚለው የአንድ ጓደኛዬ ምሬቱና ሮሮው ትዝ አለኝና በዚህች የመንግሥት ምልምል ካድሬ ድፍረትና ንቀት እጅጉን አፈርኩ፣ አዘንኩም፡፡
ክርክራችንና ሙግታችንን ስታዳምጥ የነበረችው መኪና አደጋ የደረሰባት ጓደኛችን በአልጋዋ ላይ ሆና እየተሳቀቀችና የቁስሏን ጥዝጣዜ እንደምንም ውጣ በዓይኗ ጓደኛዬን እየጠቀሰችው ወሬ እንዲቀይር ምልክት ሰጠችው፡፡ ይህች ልማታዊ ካድሬ ግን እንዲህ በቀላል ልትተውን አልፈለገችም፡፡
የእውቀቷን ጥግ ከአፍሪካ እስከ መካለኛው ምሥራቅ፣ አሜሪካና አውሮፓ ድረስ በመሻገር ልታስረዳን ዋተተች፡፡ ቀንድና ጅራቱ የማይለይ ከእኔ በላይ አዋቂ በሚል ታብዮ የፖለቲካ ትንታኔዋ ስሰማና፣ እኛኑ ለማሳመን የሄደችውን ርቀትና ከንቱ ጥረቷን ሳይ ለሷም፣ ይህችን ሴት ለመለመለው የፓርቲዋ የነገ ዕጣ ፈንታው አዘንኩኝ፡፡ ለነገሩ ኢህአዴግ በአንድ ወቅትም ሁለተኛ ክፍል ቢሆንም ፖለሲያችንን እስካስፈጸም ድረስ ችግር እንደሌለበት በግልጽ ነግሮንስ የለ፣ እናም አንፈርድበትም፡፡
‹‹ከመምህሩ ደቀ መዝሙሩ›› እንዲሉ አባቶቻችን የዚህች ሴት ወሬና ፕሮፓጋንዳ እግዚኦ የአንተ ያለህ አሰኘኝ፡፡ የማታ የማታ ከዚህች የሕወሐት አባል ከሆነች ሴት ጋር የነበረንን ውይይት ምሽቱ እየገፋ በመምጣቱ ወሬያችንን፣ ሙግታችንን ቋጭተን መለያየት ግድ ሆነብን፡፡ እናም በሕመምና በሥቃይ ውስጥ የነበረችውን ጓደኛችንን ጥቂት አዋርተናት፣ አጽናንተናት ተሰናብተናቸው ከጓደኛዬ ጋር ጉዞአችንን ወደቤታችን አደረግን፡፡ ወደቤት እየሄድን ሳለንም ጓደኛዬ እንዲህ አለኝ፡፡
ምን ዓይነት ቀን ዛሬ!! ጠዋት ቢሮ እንደገባሁ የሥራ ባልደረባዬ የሆኑ ቀንደኛ የወያኔ ደጋፊ የሆኑ ሰው ጋር ፌስ ቡኬን ከፍቼ በሊቢያ በአይ ኤስ ታረደው ሰማዕት የሆኑትን ወገኖቻችንን ምስል ሳሳያቸው ኢትዮጵያኖች ላይሆኑ ይችላሉ፣ ኤርትራዊ ወይም ሱማሌያውያን ሊሆኑ ቢችሉስ፣ ደግሞስ እነዚህ ወጣቶች በሰው አገር ከሚንከራተቱ አገራችን በዕድገት ላይ ነች፣ በርካታ ስራ ዕድል አለ ለምን በአገራቸው አይሠሩም እያሉ በወገኖቻችን ደም ላይ ሲሳለቁና ውስጤን ሲያበግኑት ዋሉ፡፡
‹‹አንበሳን ፈርቼ ዛፍ ላይ ብወጣ ነብር ጠበቀኝ›› እንዲሉ አበው ይኸው ደግሞ በዚህ ምሽት እሳት የላሰች እፍረትና ይሉኝታ የሚባል ነገር ጨርሶ የፈጠረባት የማትመስል እሳት የላሰች ካድሬ ስትሞግተን፣ ስታደርቀን አመሸች፡፡ ግን እነዚህ ሰዎች እንዴት ነው የሚያስቡት አለኝ እጅጉን አዝኖ፡፡ እንደው ፍቅር፣ ሰብአዊነትና ርኅራኄ የሚባል ነገርስ አያውቁም ማለት ነው፡፡ ሲል መልሶ እኔኑ በመገረም ሆኖ ጠየቀኝ፡፡ ወዳጄ ተወኝ ባክህ እኔም ውስጤ አሯል፣ ተኮማትሯል በማለት ልማታዊው የሃይገር ባሱ ሹፌር ጋር የገጠምኩትን አተካራዬን በአጭሩ ተረኩለትና ተሰነባብተን ተለያየን፡፡
ይህ የእኔና ጓደኛዬ ገጠመኝ መንግሥታችን ለሚመራው፣ ለሚያስተዳድረው ሕዝብ እያሳየ ያለውን አመላከት የሚያንጸባርቅ ለመሆኑ አያጠያይቅም፡፡ ሕዝብ ደስታውንም ሆነ ኀዘኑን በቅጡ የሚጋራው መሪ ይፈልጋል፡፡ ከሰሞኑ በሀገራችን ላይ በደረሰው መሪሪ ኀዘን ግን ከመንግሥት በኩል እየተስተዋለ ያለው ነገር ሆድ የሚያስብስና ቁጣን የሚቀሰቅስ እየሆነ ነው፡፡ እናም በሥልጣን ላይ ላሉ መሪዎቻችንን ይህን ጥያቄ ደጋግመን ለመጠየቅ እንገደዳለን፡፡ ለምንድን ነው መሪዎች ለምትመሩት፣ ለምታስተዳድሩት ሕዝብ ፍቅር፣ ክብርንና ሰብአዊ ርኅራኄን የጎደላችሁ፣ የተራቆታችሁ፡፡ ለምንድን ነው ለሕዝባችሁ ጥያቄ፣ ቁጣና የእኛንም አድምጡን መልእክቱ ሁሌም እልክና ማስፈራራት የሚቀድማችሁ፡፡
በኃይልና በማስፈራራትስ እስከ መቼ ለመዝለቅ ይቻላችሁ ይሆን?! በሕዝባቸው ዘንድ ‹‹ታላቁ ነፍስ›› በመባል የሚሞካሹት ዕውቁ ታጋይና የህንድ የነጻነት አባት ማሕተመ ጋንዲ፣ ‹‹ከፍርሃት ከሚመነጭ ዐምባገነንነትና ጥላቻ ከሠለጠነበት ኃይል ወይም ሥልጣን ይልቅ ከፍቅር የሚመነጭ ሥልጣን ውጤታማና ዘላቂ እንደሆነ›› በአንድ ወቅት ተናግረው ነበር፡፡
በእውነትም ሕዝብን በመልካም ለመምራት፣ ለማገልገል ሥልጣንን የሚገራ፣ ልጓም ኾኖ የሚቆጣጠር የፍቅር ልብ፣ ቅን ልብ ያስፈልጋል፡፡ የደቡባዊቷ አፍሪካ አገር የማላዊ የመጀመሪያ የሴት ፕሬዝዳንት የነበሩት ጆሴ ባንዳ፣ በአፍሪካዊው ብርቅዬ ልጅ በማዲባ የለቅሶ ስን ሥርዓትና ሽኝት ላይ ባደረጉት ንግግራቸው፡- Leadership is falling lin love with the people you lead or serve ሲሉ ተናግረው ነበር፡፡ ይህን ቅን የሆነ ፍቅር ልብ ያልታደሉ፣ ከበጎነት ጋር የተፋቱ፣ ክፋትና ጭካኔ የነገሠባቸው መሪዎች በታሪክ ደጋግመን እንዳየነው የሥልጣናቸው/የኃይላቸው ምንጭ ፍርሃት የሚወልደው ጭካኔና ማንአለብኝነት/አምባገነንነት ነው፡፡ በመጨረሻም በግፍ ለተሰዉ ወገኖቻችን ፈጣሪ አምላክ የእረፍት ቦታን ያድላቸው! ለእኛና ለሕዝባችንም ፈጣሪ ጽናትንና መጽናናትን ያድልን ዘንድ በመመኘት ልሰናበት፡፡