“አሁን ግን ክርስቶስ ላነቀላፉት በኩራት ሆኖ ከሙታን ተንስቷል። ሞት በሰው በኩል ስለመጣ ትንሣኤ ሙታን በሰው በኩል ሆኖአልና።”
(1ኛ ቆሮ. 15፡ 20-21)
የ2007 ዓ.ም የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ በዓል በመላው ኢትዮጵያ የክርስትና እምነት ተከታዮች እና በመላው ዓለም የሚኖሩ ትውልደ ኢትዮጵያውያኖች ዘንድ በደማቅ ሁኔታ ተከብሮ ውሏል። በክርስትና እምነት በተለይ በአገራችን ኢትዮጵያ እና በመላው ዓለም የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ዘንድ በየዓመቱ በታላቅ ሥነ ስርዓት የሚከበረው ይህው የትንሳኤ በዓል በትናንትናው እለት ሌሊት በየአብያተ ክርስቲያናት በተለያዩ የመንፈሳዊ ዝግጅቶች እና የጸሎት ስነ ስርአት በደመቀ ሁኔታ መከበሩ ታውቋል።
ይህንኑ በዓል በተመለከተ በውጭው ዓለም የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በዓሉን በስደት በሚኖሩባቸው ከተሞች በትናንትናው አለት በደመቀ ሁኔታ ያከበሩ ሲሆን በካናዳ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የመንበረ ብርሃን ቅድስት ማርያም ካቴድራል ቶሮንቶ የነበረውን አከባበር በተመለከተ የደርሰን ልናካፍላችሁ ወደድን። (ፎቶግራፎች ይዘናል)
በቶሮንቶ የመንበረ ብርሃን ቅድስት ማርያም ካቴድራል የበዓል ዝግጅት መርሃ ግብር መሰረት ትናንት ቅዳሜ ሚያዝያ 3 ቀን 2007 ዓ. ም. ከምሽቱ 6፡00 ሰአት እስከ ሌሊቱ 1:30 ሰዓት ድረስ ብጹእ አቡነ ዲሞጥርዮስ የካናዳ – ኦንታሪዮ ሐገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና እጅግ በጣም በርካታ የቶሮንቶ እና የአካባቢው ምእመናን በተገኙበት እና እጅግ ደማቅ በሆነ በተለያዩ መንፈሳዊ ዝግጅቶች፤ የወንጌል ትምህርት፤ ማህሌት፤ ጸሎት ወንጌል ምስባክ፤ ኪዳን እና በመጨረሻም የቅዳሴ ሥነ ስርአት ተክበሮ ውሏል።
በቶሮንቶ የመንበረ ብርሃን ቅድስት ማርያም ካቴድራል ሥነ ስርአት ላይ ብጹእ አቡነ ዲሞጥርዮስ የካናዳ – ኦንታሪዮ ሐገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በበአሉ ላይ በመገኘት ለተሰበሰበው ምእመናን ቃለ ቡራኬ የሰጡ ሲሆን የጸሎት ሥነ ስራአቱን በመምራት፤ ለምእመናኑ መንፈሳዊ ትምህርትም ሰጥተዋል። በዝግጅቱ ላይ በበዓሉ የነበሩ ምዕመናን የጧፍ ማብራት ሥነ ስርአት የተካሄደ ሲሆን የደብሩ ታዳጊ መዘምራን “ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ” ወረብ በማቅረብ ለበዓሉ ትልቅ ድምቀት ሰጥተውታል።
በካናዳ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ዋና አስተዳዳሪ የሆኑት ሊቀ ካህናት ምሳሌ እንግዳ በዓሉ ሰላምንና ፍቅርን የሚሰጥ ይሁንልን ዘንድ እኗኳን ለብርሃን ትንሳኤው አደረሳችሁ በማለት ለምእመናኑ አጠር ያለ መንፈሳዊ መልእክት አስተላልፈዋል።
በዚህ የትንሳኤ በዓል ዝግጅት ላይ ለየት የሚያደርገው የቤተክርስቲያኑ የበአል ዝግጅት ኮሚቴ በጣም ሊደነቅ እና ሊመስገን ይገባዋል። ምእመናን ለበዓሉ ዝግጅት ወደ ቤተክርስቲያኑ ባመሩበት ወቅት ከመኪና ማቆሚያ አንሰቶ በቤተክርስቲያኑ በዓሉን ለማክበር የተመመውን በብዙ ሺህ የሚቆጠር ምእመናን ቦታ በማስያዝ፤ ፕሮግራሙን በመምራት እና ሥርዓት በማስያዝ ያደርጉት ጥረት እና የተሳካ ዝግጅት በጣም የሚያስመሰግን እና ለሌሎች ጥሩ ትምህርት እና አርአያ ሊሆን የሚችል መሆኑን ተገንዝበናል!!
በዚህ አጋጣሚ -የአቡጊዳ ድህረ ገጽ ዝግጅት ክፍልም እንኳን ለብርሃነ ትንሳኤ በዓል በሰላም አደርሳችሁ እያለ ለመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች በዓሉ የሰላም እና የፍቅር እንዲሆንላችሁ መልካም ምኞቱን ይገልጻል!